2018-01-01 16:31:00

ታህሣሥ 22 ቀን 2010 ዓ.ም. ቃለ እግዚኣብሔር እና አስተንትኖ በክቡር አባ ግርማቸው ተስፋዬ።


ታህሣሥ 22 ቀን 2010 ዓ.ም. ቃለ እግዚኣብሔር እና አስተንትኖ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ካህን በሆኑት በክቡር አባ ግርማቸው ተስፋዬ።

የዚህን አስተንትኖ ሙሉ ይዘት ከዚህ በታች ያለውን ተጫወት  የሚለውን ምልክት በመጫን ማዳመጥ ትችላላችሁ!

የእለቱ ምንባባት

ዕብራዊያን  1316-25

ደግሞም መልካም ማድረግንና ያላችሁንም ከሌሎች ጋር መካፈልን አትርሱ፤ እግዚአብሔር ደስ የሚሰኘው እንደዚህ ባለው መሥዋዕት ነውና። ለመሪዎቻችሁ ታዘዙ፤ ተገዙላቸውም። ምክንያቱም እነርሱ በብርቱ የሚያስጠይቃቸው ነገር ስላለባቸው፣ ስለ ነፍሳችሁ ጒዳይ ይተጋሉ። ስለዚህ ሥራቸውን በሐዘን ሳይሆን በደስታ ማከናወን እንዲችሉ ታዘዟቸው። አለበለዚያ አይበጃችሁም።

ለእኛ ደግሞ ጸልዩልን። በሁሉም መንገድ በመልካም አኗኗር ለመኖር የሚናፍቅ ንጹሕ ኅሊና እንዳለን ርግጠኞች ነን። በተለይም ወደ እናንተ በፍጥነት ተመልሼ እንድመጣ ትጸልዩል ዘንድ ዐደራ እላችኋለሁ። በዘላለም ኪዳን ደም የበጎች ታላቅ እረኛ የሆነውን ጌታችን ኢየሱስን ከሞት ያስነሣው የሰላም አምላክ፣ ፈቃዱን እንድታደርጉ በመልካም ነገር ሁሉ ያስታጥቃችሁ፤ ደስ የሚያሰኘውንም በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በእኛ ያድርግ፤ ለእርሱ እስከ ዘላለም ድረስ ክብር ይሁን፤ አሜን።

ወንድሞች ሆይ፤ የጻፍሁላችሁ መልእክት አጭር እንደ መሆኑ፣ የምክር ቃሌን በትዕግሥት እንድትቀበሉ ዐደራ እላችኋለሁ። ወንድማችን ጢሞቴዎስ እንደተፈታ ታውቁ ዘንድ እፈልጋለሁ፤ ቶሎ ከመጣ፣ ከእርሱ ጋር ላያችሁ እመጣለሁ። ለመሪዎቻችሁ ሁሉና ለቅዱሳን ሁሉ ሰላምታ አቅርቡልኝ። ከኢጣሊያ የሆኑትም ሰላምታ ያቀርቡላችኋል። ጸጋ ከሁላችሁ ጋር ይሁን።

 

1 ጴጥሮስ 221-25

የተጠራችሁትም ለዚሁ ነው፤ ምክንያቱም ክርስቶስ ስለ እናንተ መከራን የተቀበለው የእርሱን ፈለግ እንድትከተሉ ምሳሌን ሊተውላችሁ ነው። “እርሱ ኀጢአት አላደረገም፤ በአፉም ተንኰል አልተገኘበትም።” ሲሰድቡት መልሶ አልተሳደበም፤ መከራ ሲደርስበት አልዛተም፤ ነገር ግን በጽድቅ ለሚፈርደው ራሱን አሳልፎ ሰጠ። ለኀጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር እርሱ ራሱ በሥጋው ኀጢአታችንን በእንጨት መስቀል ላይ ተሸከመ፤ በእርሱ ቊስል እናንተ ተፈውሳችኋል። ቀድሞ እንደ ጠፉ በጎች ትቅበዘበዙ ነበር፤ አሁን ግን ወደ ነፍሳችሁ እረኛና ጠባቂ ተመልሳችኋል።

የዮሐንስ ወንጌል 101-12

እረኛና መንጋው

“እውነት እላችኋለሁ፤ ወደ በጎች ጒረኖ በበሩ ሳይሆን፣ በሌላ በኩል ዘሎ የሚገባ ሌባና ነጣቂ ነው፤ በበሩ የሚገባ ግን እርሱ የበጎቹ እረኛ ነው፤በር ጠባቂው በሩን ይከፍትለታል፤ በጎቹም ድምፁን ይሰማሉ። የራሱንም በጎች በየስማቸው እየጠራ ያወጣቸዋል። የራሱ የሆኑትንም ሁሉ ካወጣ በኋላ ፊት ፊታቸው ይሄዳል፤ በጎቹም ድምፁን ስለሚያውቁ ይከተሉታል።እንግዳ የሆነውን ግን ድምፁን ስለማያውቁ ከእርሱ ይሸሻሉ እንጂ ፈጽሞ አይከተሉትም።” ኢየሱስ ይህን ምሳሌ ነገራቸው፤ እነርሱ ግን ምን እንደ ነገራቸው አላስተዋሉም።

ስለዚህ ኢየሱስ ዳግም እንዲህ አላቸው፤ “እውነት እላችኋለሁ፤ የበጎች በር እኔ ነኝ። ከእኔ በፊት የመጡት ሁሉ ሌቦችና ቀማኞች ነበሩ፤ በጎቹ ግን አልሰሟቸውም። በሩ እኔ ነኝ፤ በእኔ በኩል የሚገባ ሁሉ ይድናልይገባል፤ ይወጣልም፤ መሰማሪያም ያገኛል። ሌባው ሊሰርቅ፣ ሊገድልና ሊያጠፋ ብቻ ይመጣል፤ እኔ ግን ሕይወት እንዲኖራቸውና እንዲትረፈረፍላቸው መጥቻለሁ።”

“መልካም እረኛ እኔ ነኝ፤ መልካም እረኛ ሕይወቱን ስለ በጎቹ አሳልፎ ይሰጣል፤ ተቀጣሪው እረኛ ግን በጎቹ የእርሱ ስላልሆኑ፣ ተኵላ ሲመጣ ጥሎአቸው ይሸሻል፤ ተኵላውም በጎቹን ይነጥቃል፤ ይበትናቸዋልም።

 

ታህሣሥ 22 ቀን 2010 ዓ.ም. ቃለ እግዚኣብሔር እና አስተንትኖ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ካህን በሆኑት በክቡር አባ ግርማቸው ተስፋዬ።

 

በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተወደዳችሁ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች እንዲሁም በጎ ፈቃድ ያላችሁ ሁሉ ዛሬ እንደ ቤተክርስቲያናችን ሥርዓት አቆጣጠር ዘኖላዊ ወይንም ዘስብከት 3ኛ ሰንበትን እናከብራለን ፡፡ በዚህም ሰንበት በቤቱ የሰበሰበን ቃሉንም እንድንሰማ ፈቃዱ የሆነ አምላካችነ ከዘለዓለም እስከ ዘለዓለም የተመሰገነ ይሁን፡፡

የመጀመሪያው የዕብራውያን መልእክት እግዚአብሔርን ደስ ስለሚያሰኘው መስዋዕት ይናገራል፡፡  ይህንንም “ወንድሞቼ ሆይ የፃፍሁላችሁ መልዕክት አጭር እንደመሆኑ የምክር ቃሌን በትዕግሥተ እንድትቀበሉ አደራ እላችኋለው”ይላል ዕብ. 16.22

የዚህ የዕብራውያን መልዕክት ጸሐፊ በውል ባይታወቅም ይህ መልዕክት ለዕብራውያን ያደርሳል፡፡  በመጀመሪያ ደረጃ የዘለዓለምን ሕይወት ለመውረስ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መንገድ ብቻ መጓዝ እንዳለባቸው በ2ኛ ደረጃ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መንገድ መጓዝ የማያልቅ በረከት በሕይወታቸው እንደሚሰጣቸው በ3ኛ ደጃ በጌታችን ኢየሱሱ ክርስቶስ መንገድ መጓዝ በውስጡ ወይንም በጉዞው ላይ ብዙ መስቀል መኖሩን እንዲገነዘቡና ይህንንም መስቀል በትዕግሥትና በጥበበ መሸከም እንዳለባቸው ለማሳሰብ በመጨረሻም እግዚአብሔር ለእነሱ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በኩል የሰጣቸውን አዲስ የሕይወት ጉዞ አዲስ የክርስትና ጉዞ በመተው ወደ ቀድሞው ኃጢያትና ክፉ ሥራ ከተመለሱ ብርቱ ቅጣት ወደ ፊት እንደሚጠብቃቸው ያሳስባቸዋል፡፡

ይህ ማሳሰቢያ በእርግጥ ለእነርሱ ብቻ ሳይሆን ዛሬ በቀጥታ እኛን እያንዳንዳችንን ይመለከታል፡፡

ሁላችን በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚገኘውን ደህንነት ብቻ በማሰብ በእርሱ ብቻ በመታመንና ለቃሉ በመገዛት መኖር እንዲሁም እርሱን ስንከተል እርሱ ራሱ ያለፈባቸውን የመስቀል መንገዶች ሁሉ በፅናት በመከተል እንድንጓዝ ያስፈልጋል፡፡

እግዚአብሔር ከእኛ የሚፈልገው በቃላችን የምናቀርበውን ጸሎት ብቻ ሳይሆን ዘወትር ይህንንም ቃል በተግባራችን እንድናውለው የፈልጋል፡፡

ልክ በኦሪት ዘመን እንደነበረው የእንስሳትን ደም በማፍሰሰ ብቻ የምናቀርበውን መሥዋዕት ሳይሆን ወንድሞቻችንን እና እህቶቻችንን በመርዳት ፍቅርን ምሕረትን ይቅርታ አድራጊዎችም እንድንሆን ያስፈልጋል፡፡ በእግዚአብሔር አብ ፊት ንጹህና ነውር የሌለበት ሃይማኖት ይህ ነው ሰውን ሁሉ በችግሩ መርዳትና፡ ከዓለም እርኩሰት ራስን መጠበቅ ነው ይላል ቅዱስ ሐዋርያው፡ ያዕቆብ 1፡27፡፡

እግዚአብሔር መስዋዕት አድረገን እንድናቀርብለት የሚያስፈልገው ንጹህ ልባችንን ነው ከኃጢያት በመራቅ የተቀደሰውን የእኛን ሰውነት ነው (ሮሜ. 12፡1) እንዲህ ይለል “”እንግዲህ ወንድሞች ሆይ ሰውነታችሁን ቅዱስና እግዚአብሔርን ደስ የሚያኝ ሕያው መስዋዕት አድረጋችሁ ታቀርቡ ዘንድ በእግዚአብሔር ርኀራኄ እለምናችኋለው፡፡

በሁለተኛው መልእክት ቅዱስ ሐዋርያው ጴጥሮስ በመጀመሪያ መልዕክቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህንን ሁሉ መከራና ስቃይ የተቀበለው ለእኛ ምሳሌ ለመሆን እንደሆነ ይናገራል፡፡

የክርስትና ጉዞ ይሄ ነው ልክ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳስተማረን የትኛውንም ክፉ ነገር በመልካም መመለስ፡፡ ለዚህም እሱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አይነተኛ ምሳሌያችን ነው በትንቢተ ኢሳያስ 53፡7 እንዲህ ይላል “ተጨነቀ ተሰቃየም ነገር ግን አፉን አልከፈተም እንደ ጠቦትም ለእርድ ተነዳ በሸላቾች ፊት ዝም እደሚል በግ አፉን አልከፈተም፡፡”

የክርስቶስን መንገድ ለመከተል ጉዞ ከጀመርን እኛም በሚደርስብን መከራና ሥቃይ የእርሱን ፈለግ መከተል የግድ ነው ምክንያቱም ያለ ስቃይና ያለ ችግር ያለ ብዙ ፈተና ወደ ዘለዓለማዊ ክብር ለመድረስ አንችልም፡፡ (ሮሜ. 6፡5)እንዲህ ይላል “በሞቱ ከእርሱ ጋር እንዲህ ከተግባርን በትንሣኤውም በእርግጥ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን፡፡”

ጌታችን ኢየሱሱ ክርስቶስን ስንከተል በሚደርሰስብን መከራና እንግልት ተስፋ ልንቆርጥ አይገባንም ምክንያቱም እኛም የዘለዓለምን ሕይወት ያገኘነው ፣ ከኃጢያት ሠንሠለት የተፈታነውና የተፈወስነው በእርሱ ቁስል ነውና፡፡  ትንቢተ ኢሳያስ 53፡5 ላይ እንዲህ ይለል “ነገር ግን እሱ ስለመተላለፋችን ተወጋ ስለ በደላችንም ተደበደበ በእርሱ ላይ የወደቀው ቅጣት ለእኛ ሰላም አመጣልን በእርሱም ቁስል እኛ ተፈወስን፡፡”

ዘወትር ጠባቂያችንና እረኛችን ጌታችን ኢየሱሱ ክርስቶስ በዚህ ሁሉ መከራው እኛን በጸጋው በኃይሉ አበርትቶናልና በዚሁ ኃይል በምናገኘው እርዳታ የሰይጣንን ፈተናና ዓለምን በማሸነፍ ከእርሱ የወረስነውን መልካም አብነት በሕይወታችን በዕለት ተዕለት ጉዟችን ተግባራዊ እንድናደርግ ያስፈልጋል፡፡

በዮሐንስ ወንጌል 10፡1-12 ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ መልካም እረኛ ያስተምረናል፡፡

በብሎይ ኪዳን እግዚአብሔር የእስራኤላውያን እረኛ እንደነበር በመዝ. 23፡1 እንደሁም በትንቢተ ሕዝቅኤል 34፡11-12 ይናገራል “እግዚአብሔር እረኛዬ ነው እንዳች አይጐድልብበኝም” (መዝ. 23፡1) “ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ የለልና እኔ ራሴ በጐቼን እፈልጋቸዋለው እጠብቃቸዋለሁም እረኛ ከመንጋው ጋር ሳለ የተበተኑትን በጐች እንደሚፈልግ ሁሉ እኔም በጐቼን እፈልጋቸዋለው”

በአዲስ ኪዳን ውስጥ ደግሞ እግዚአብሔር ይህንን የእረኝነትን ሥራ ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አውርሶታል፡፡ ለዚህ ነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቴስ በዮሐ. 10፡11 ላይ “መልካም እረኛ እኔ ነኝ መልካም እረኛ ሕይወቱን ስለ በጐቹ አሳልፎ ይሰጣል”ብሎ የናገረው፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እውነተኛ የሕይወት መንገድ እውነተኛ የሕይወት በር ነው፣、የትኛውንም ዓይነት መልካም ሥራ ለመሥራት እንዲሁም ወደ የቅድስና ሕይወት ለመግባት የግድ የሕይወት በር በሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ማለፍ ያስፈልጋል፡፡

ከዚህ እውነተኛ ከሆነው የሕይወት በር በስተቀር ሌላ የቅድስና መግቢያ በር የለም በሌላ በር ለመግባት የሚሞክር ሁሉ ሐሰተኛ ነው  ምክንያቱም በሌላ በር በኩል ገብቶ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ጸጋና በረከት መቀበል የሚችል ማንም የለም፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእርሱ በኩል እንድናልፍ የሚፈልገው የተትረፈረፈ ሕይወት እንዲኖረን ነው  የተትረፈረፈ ሕይወት እንድናገኝ ነው፡፡  ስለዚህ ሁላችንም በእርሱ በኩል በማለፍ የተቀደሰና በእርሱ ጸጋ የተሞላ አዲስ ሕይወት ይዘን ወደ ቅድስና ጉዞአችንን እንደናጠናክር ያስፈልጋል፣ ለዚህም የደካሞች እናት የሃዘነተኞች አፅናኝ የሆነች እናታችን እመቤታችን ቅድስት ድንገል ማርያም ትርዳን ጸጋና በረከቱን ከልጇ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ታሰጠን፤የሰማነውን በልባችን ያኑርልን፡፡

 

 

 

 

 








All the contents on this site are copyrighted ©.