2012-12-08 09:54:18

4ኛ ሰንበት ዘአስተምህሮ 2005 ዓ.ም.(9.12. 2012) ሰንበት ዘመጻጕዕ


መዝሙር፡ ይቤሉ እስራኤል ኢርኢነ ወኢሰማዕነ. . . .
ንባባት፡ 1ቆሮ. 2፡1~ፍ፥ 1ዮሓ፡ 5፡1~6፥ ግ.ሓ.5፡34~ፍ፥ ዮሓ. 9፡1~ፍ።
ስብከት፡ ደቂቀ እጓለ እመሕያው እስከ ማእዜኑ ታከብዱ ልበክሙ ለምንት ታፈቅሩ ከንቶ ወተሐሱ ሐሰተ፥ አእምሩ ከመ ተሰብሓ እግዚአብሔር በጽድቁ።” መዝ.4፡2።

የዛሬው ወንጌል ስለ አንድ ዕውር ሆኖ ስለተወለደ እና ክርስቶስ ዓይኖቹን ጭቃ ቀብቶ ስለፈወሰው ሰው ይናገራል፡፡ (ዮሐ. 9፡1-41)
RealAudioMP3 ይህ ተዓምር በዘመኑና በቦታው በነበሩት ሰዎች ውስጥ የተለየ ስሜትን ፈጥሯል፡፡
    በተራው ሕዝብ ውስጥ የመደናገርን ስሜት አሳድሯል፤ ከሚለምንበት ሥፈራ ተነስቶ፣ ያለ መሪ ሲመላለስ በማየታቸው ግራ ተጋቡ፣ ተደናገጡ፤ ምክንያቱም በሕይወት ዘመናቸው እንዲህ ያለ ድንቅ ነገር አይተው አያውቁምና፡፡ ስለዚህ ምስክርነት ከመስጠት እና እግዚአብሔርን ከማክበር ይልቅ ሰውየውን ወደ ፈሪሳውያን መውሰድ መረጡ፡፡
    ፈሪሳውያንም በበኩላቸው የዚህ ምስኪን ሰው ፈውስ ማግኘት ግድ ሳይላቸው በአንጻሩ ጭራሸ በተለያየ ጥያቄ እያደናገሩ የፈወሰውን ኢየሱስን እንዲክድ፣ ልክ እንደነሱ አዳኙን የእግዚአብሔርን አንድያ ልጅ “ኃጢአተኛ” እንዲል ይገፋፉት ጀመር፡፡ ይህ ስላልሆነላቸውም ከምኵራባቸው አባረሩት፡፡
    የዳነው ሰው ወላጆችም ቢሆኑ ከፍርሀት የተነሳ ምስክርነት መስጠት ስላልፈለጉ ኃላፊነቱን ልጃቸው እንዲወጣው ብለው “እርሱ ሙሉ ሰው ነውና ስለሆነው ነገር ራሱ ይመልስ ዘንድ እሱኑ ጠይቁት” በማለት ወደ ኋላ አፈገፈጉ፡፡
    ድንቅ የተደረገለት ዓይነ ስውር ግን ያለ ምንም ፍርሃት ጌታውን እና የብርሃን አምላክ የሆነውን ኢየሱስን ማክበር ስለሱም መመስከርን መረጠ፡፡

ከዛሬው ወንጌል ምን እንማራለን?
ማንም ሰው “ለምን እንዲህ ሆኜ ተፈጠርኩ፣ ለምን ይህ ዓይነት ጠባይ ኖረኝ ወዘተ” ብሎ ረብ የሌው ጥያቄ ከማንሳት ይልቅ ማስተካከል እና ማሳመር፣ የሰውን ሕይወት እነዲሻሻል እና እንዲለወጥ ወደሚፈቅደውና በባሕሪው አምላክ ወደሆነው ፈጣሪ መጠጋት ነው፡፡
እምነታችን ብዙ ጊዜ ይፈተን ይሆናል፤ የስራ፣ የትምመህርት፣ የሕይወት አለመሳካት ብዙ ጊዜ የእምነታችንን አቅም ጥያቄ ውስጥ ገብቶ ይሆናል፡፡ ዓመቱ የእምነት ዓመት ተብሎ ተወስኗልና በዚህ በጸጋ ዓመት እንጠቀምበት፡፡ ዓይነ ስውሩ ማየት ተመኘ ይህ መሻቱም እውን ሆነለት፡፡ እኛስ ምን እንዲደረግልን ነው የምንፈልገው? የልባችንን መሻት ስንለምን ግን ባልተከፋፈለ ወይም በጎዶሎ እምነት መሆን የለበትም፣ ጠንካራ እምነት ነው ወደ ፈውስ እና ወደ ስኬታማነት የሚያመጣን፡፡ አንድ ጸጋ ስንጠይቅ ሌላ መማር የሚገባን ነገር ቢኖር ትዕግስት ነው፤ “መጠበቅ” የሚባለውን ነገር መማር እና መለማመድ ይኖርብናል፣ “በለስን የጠበቀ ፍሬዋን ይበላል” እንዲል መጽሐፍ (መጽ. ምሳሌ 27፡18)፡፡ ሁሉ ነገር የሚሆነው እግዚአብሔር ሲወድ እና ሲፈቅድ ብቻ ነው፡፡
የእግዚብሔር ጥበቃ እና የእመቤታችን ቅድሰት ድንግል ማርያም አማላጅነት ከሁላችሁ ጋር ይሁን!

አባ ዳዊት ወርቁ
ዘማኅበረ ካፑቺን








All the contents on this site are copyrighted ©.