2018-07-06 10:25:00

ሽብርተኝነት በማህበራዊ አንድነትና መግባባት ይሸነፋል ተባለ።


ሽብርተኝነት በማህበራዊ አንድነትና መግባባት ይሸነፋል ተባለ።

ሽብርተኝነት በማህበራዊ አንድነትና መግባባት እንደሚሸነፍ፣ በተባበሩት መንግሥታት የቅድስት መንበር ቋሚ ታዛቢ የሆኑት ሞንሲኞር ቤርናዲቶ አውዛ አስገነዘቡ። ይህን ተግባራዊ ለማድረግ ይቻል ዘንድ ማሕበራዊ መግባባትንና አንድነትን የሚያጠናክሩ የፖለቲካ ስርዓቶችን መዘርጋት እንደሚያስፈልግ ሞንሲኞር ቤርናዲቶ አውዛ ተናግረዋል። 

ከዚህም ጋር ሰብዓዊ መብቶችን የሚያስከብሩ ዓለም ዓቀፍ ድንጋጌዎችን ማክበር እጅግ አስፈላጊ እንደሚሆን ሞንሲኞር ቤርናዲቶ አውዛ ገልጸዋል። ዓለም ዓቀፍ ሰብዓዊ መብቶችን ማክበር፣ ሽብርተኞችም ሰብዓዊ መብቶችን እንዳይተላለፉ እና የሽብር ተግባራቸውን እንዳያስፋፉ ያግዳቸዋል ብለዋል። ሰኔ 23 ቀን 2010 ዓ ም በኒዮርክ በተካሄደው የተባበሩት መንግሥታት ጉባኤ፣ ብጹዕ ሞንሲኞር ቤርናዲቶ አውዛ እንዳስገነዘቡት፣ በሰላምና በደህንነት ላይ የሚቃጣውን አደጋ ለመዋጋት የተባበሩት መንግሥታት ስብዓዊ መብቶችን ማክበር ብቻ ሳይሆን የተለያዩ አገሮች መንግሥታት ተዳምረው በጋር መስራት እጅግ አስፈላጊ እንደሆነ አስረድተዋል። ሞንሲኞር ቤርናዲቶ አውዛ በማከልም ቅድስት መንበርም ከሌሎች የሐይማኖት መሪዎች ጋር በመተባበር ሽብርተኝነት እንዳይስፋፋ ያላሰለሰ ጥረት በማድረግ ላይ መሆኗን ተናግረአዋል።

የተባበሩት መንግሥታት ባዘጋጀው በዚህ ጉባኤ ላይ የተለያዩ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሁኑ ተቋማት ተሳትፈዋል። በውይይታቸው ወቅትም ሽብርተኝነትን ለመዋጋት መንግሥታት በምን መንገድ ቢተባበሩ መልካም ይሆናል በሚሉ ሃሳቦች በስፋት ተወያይተዋል። ሞንሲኞር ቤርናዲቶ አውዛ ባቀረቡት አስተያየት ውስጥ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት ማሕበራዊ ውሕደት አንዱ መንገድ ነው የሚል ሃሳብ ይገኝበታል። ከዚህ ጋር ተያይዞ በሕብረተሰብ መካከል እያደጉ ለሚመጡ ችግሮች የመጨረሻ መፍትሄው ሽብርን መቀስቀስ ነው ብለው የሚያስቡ የሕብረተ ሰቡ ክፍሎችን፣ አለ የሚሉ ችግሮች የትኞቹ እንደሆኑ በጽሞና ማዳመጥና በአፋጣኝ እነዚያን ችግሮች ማቃለል ያስፈልጋል ብለዋል። በተጨማሪም ከሕብረተሰቡ ዘንድ የሚፈልቁ አዲስ ርዕዮተ ዕለማዊ አስተሳሰቦችን ለውይይት አቅርቦ በመወያየት መልስ ለማግኘት መንግስታት እገዛ ማድረግ እንደሚያስፈልግ እና ስለ ሰብዓዊ መብቶች ሕዝብ በቂ ግንዛቤን እንዲጨብጥ ማድረግ እጅግ አስፈላጊ እንደሆነ ብጹዕ ሞንሲኞር ቤርናዲቶ አውዛ አስገንዝበዋል። በዚያኑ መጠን ሕብረተ ሰቡ ስለ ሰብዓዊ መብት ጠንቅቆ ማወቅ፣ መንግሥታትም ጭምር ሰብዓዊ መብቶችን እንዲያከብር ያስገድዳል ብለዋል። ሞንሲኞር ቤርናዲቶ አክለውም በግለ ሰብ ደረጃ ይሁን በቡድን ሆነው የሽብር ወንጀል የሚፈጽሙ ሰዎች ወደ ፍርድ ዘንድ ቀርበው ተገቢውን ፍርድ የሚያገኙበት ጠንካራ ሥርዓት መዘርጋት እንዳለበት ጠይቀዋል።

በተባበሩት መንግሥታት የቅድስት መንበር ቋሚ ታዛቢ የሆኑት ሞንሲኞር ቤርናዲቶ አውዛ አክለውም፣ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት ማሕበራዊ ውሕደት እና እያንዳንዱን የሕብረተሰብ ክፍሎችን የማሳተፍ አስፈላጊነትን በተመለከተ መንግሥትና ሐላፊነት የተሰጣቸው የአካባቢ መሪዎች፣ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት የሚረዱ እቅዶችን ለሕብረተሰቡ በማሳወቅ እና በማስተማር ሂደት እንዲሳተፉ ማድረግና የፖለቲካ ሥርዓትም ጠንካራ መሆን ያስፈልጋል ብለዋል። በመጨረሻም ዴሞክራሲያዊ ስርዓትን በማሳደግ ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብትን ማስከበር አመጽንና ጥላቻን ማስወገጃ መንገድ መሆኑን በማስገንዘብ አስተያየታቸውን አጠቃልለዋል።            

 








All the contents on this site are copyrighted ©.