2017-08-17 09:29:00

የፍልሰታ ማሪያም አስተምህሮ ክፍል ሦስት


የፍልሰታ ማሪያም አስተምህሮ ክፍል ሦስት

እንደ አገራችን ሥርዓተ አምልኮና መንፈሳዊ ልማድ በእመቤታችን በኩል እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ስለገለጠው ተስፋና በእርስዋም ጸጋ መሞላት ላደረገልን ቸርነት በተለየ ሁኔታ በየዓመቱ ለ16 ቀናት የሚዘለቀወን ጾምና ምህለላ የምናደርግበት የፍልሰታ ዘመን ላይ እንገኛለን። እግዚአብሔር አብ በእርሱ ለኖሩት ሁሉ ሊያደርግላቸው ቃል የገባውን እውነታ እርሱ በፈቀደው መልኩ በእመቤታችን የተገበረበትን ጸጋ እንወድሳለን፤ ለእኛም ይሆንልን ዘንድ “ማርያም ሆይ! ቸር፣ የሰው ልጆች ሁሉ አዳኝ ወደ ሆነው ልጅሽ ለምኝልን/ በማለት የእናትነት አማላጅነቷን የምንማጽንበት የፍልሰታ ወቅት ላይ እንገኛለን።

ከ6ኛ ክፍለ ዘመን አንስቶ እስከ ዛሬው ቀን ደረስ በምስራቃዊያን የኦርቶዶክ አብያተ ክርስቲያናትና በካቶሊክ አብያተ ክርስቲያናትም ጭምር እየተከበረ የሚገኘው ማሪያም በሥጋ እና በነፍስ ወደ ሰማይ ወጣች የሚለውና በአሁኑ ጊዜ እኛ እየጾምነው የምንገኘውን የፍልሰታ ወቅት ምንም እንኳን ከስድስተኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ እየተከበረና እየተዘከረ የሚገኝ ክብረ በዓል ቢሆንም የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ዶግማ ወይም አንቀጸ-ሐይማኖት የማይለወጥ የማይሻር አስተምህሮ ተደርጎ በቤተክርስቲያኗ ሕግጋት ውስጥ የሰፈረው ግን እንደ አሮፓዊያኑ የቀን አቆጣጠር በ1950 ዓ.ም. በወቅቱ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት በነበሩት ፒዮስ 12ኛ ከጸደቀ ቡኃላ ነው።

እንደ አውሮፓውያኑኑ የቀን አቆጣጠር በኅዳር 1/1950 ዓ.ም. ላይ በወቅቱ ያካቶሊክ ቤተክርስቲያን ሊቃነ ጳጳሳት የነበሩት ፒዮስ 12ኛ ማሪያም ምድራዊ ሕይወቷ ሲያበቃ በነብስ እና በሥጋ ወደ ሰማይ ፍልሳለች የሚለውን አስተምህሮ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ዶግማ ወይም አንቀጸ-ሐይማኖት የማይሻር የማይለወጥ አስተምህሮ እንዲሆን በደነገጉበት ወቅት ይህን አንቀጸ-እምነት በሚገባ በሚያብራራው በላቲን ቋንቋ ሙኒቼንቲሲሙስ ዴውስ በአማሪኛው በግድፉ ሲተረጎም እጹብ ድንቅ እግዚኣብሔር በተሰኘው ሐዋሪያዊ ሕግ-ጋት ላይ በቁጥር አንድ እስከ አምስት ያለውን ማሪያም ምድራዊ ሕይወቷ ሲያበቃ በነብስ እና በሥጋ ወደ ሰማይ ፍልሳለች የሚለውን አስተምህሮ በሚከተለው መልኩ ያብራራሉ።

1. እጅግ የተትረፈረፈ እና ሁሉን ቻይ የሆነው እግዚአብሄር በጥበብና በፍቅር ላይ በማትኮር፣ በእራሱ ምስጢራዊ ዓላማ በሐዘን ውስጥ የሚገኙትን የሕዝቦቹን እና ግለሰቦችን በሕይወታቸው ውስጥ ከጊዜ ወደ ጊዜ ደስታን በማኖር በተለያየ ሁኔታ እና በተለያየ መንገድ በመሥራት ለሚወዱት ሰዎች ነገሮች በመልካም ሁኔታ እንዲከናወኑ ያደርጋል” ይለናል።

2. እምቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም በክርስቶስ ደም በዳኑ ሰዎች ሁሉ ስም በመሆን የእናትነት ኃልፊነቷን በሚገባና ብቃት ባለው መልኩ በመወጣቷ የተነሳ የእርሷ ልጆች የሆንን የእኛ ልብ እና ሕሊናችን ሳይቀር ወደ እርሱ እንዲሳብ ማድረግ ችላለች።

3. እግዚኣብሔር የመረጠው እና የፈቀደ ጊዜ በደረሰ ጊዜ እርሱ በመረጣት እና በወደዳት እምቤታችን ማሪያም ላይ የመንፈስ ቅዱሱን ጥበቃ በማወረድ ምልአት ባለው መልኩ ከሴቶች ሁሉ በመምረጥ ፍጹም በሆነ ጸጋ የተሞላ ጥምረት ፈጠሩን የካቶሊክ ቤተክርስቲያን በግልጽ የምትስተምረው እውነታ ነው።

4. ለዚህም ነው እንግዲህ ቤተክርስቲያናችን በየክፍለ ዘመናቱ ይህንን የተመለከቱ ተከታታይ ጥናቶችን በማድረግ አሁንም ቢሆን ማሪያም በሥጋና በነፍስ ወደ ሰማይ እንደ ፈለሰች በማስተማር እና ይህንንም እምነት አጥብቃ በመጠበቅ የእጊግዚኣብሔር እናት የሆነችው ቅድስት ድንግል ማሪያ ሁሌም ደምቃ ትታይ ዘንድ የምትጥረው።

ከዚህ ቀደም እንደ አውሮፓዊያኑ የቀን አቆጣጠር 1854 በወቅቱ የነበሩት የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት በፒዮስ 9ኛ ማሪያም ያለ አዳም ኃጢኣት የተጸነሰች ናት የሚለውን ዶግማ ወይም አንቀጸ-እምነት የማይሻር የማይለወጥ አስተምህሮ በካቶሊክ ቤተክርስቲያን ሕግ ጋት ውስጥ እንዲካተት በማድረጋቸው የተነሳ ለማሪያም ያለው ክብር ከፍ እንዲል አድርጎታል።

ክርስቶስ በሞቱ ኃጢኣትን እና ሞትን ድል አድርጉዋል፣ ሰለዚህም በጥምቀት እንደገና የተወለዱ ሁሉ መለኮታዊ በሆነ ኃይል በክርስቶስ አማክይነት ሞትን ድል ያደርጋሉ። ነገር ግን እግዚኣብሔር የዓለም ፍጻሜ እስኪ መጣ ድረስ ሞትን ድል የመሳት ስጦታ ሙሉ በሙሉ ገቢራዊ እንዲሆን አላደረገም። ለዚህም ነው ታዲያ በጣም መልካም የሚባሉ ሰዎች ሥጋ ሳይቀር ከሞቱ ቡኃላ በድናቸው በመጨረሻው ቀን ከሙታን መነሳት በሚመጣበት ወቅት ነብሳቸው እና ሥጋቸው በታላቅ ክብር እስኪዋሃዱ ድረስ እንዲበሰብስ የሚያደርገው።

ነገር ግን እግዚኣብሔር ይህንን አጠቃላይ የሆነ ሕግ በማሪያም ላይ አልተገበረውም። እርሷ እግዚኣብሔር በሰጣት ልዩ መብት የተነሳ ከአዳም የወረስነው ኃጢኣያት ሳይነካት እንድትጸነስ በማድረጉ ኃጢኣያት እንዲነካት አላደረገም፣ በዚህም ሰበብ ሥጋዋ እንደማንኛውም ሰው በመቃብር ውስጥ እንዲበሰብስ በለመደረጉ የተነሳ ነው እንግዲህ እኛ ሁላችን እስከ መጨረሻው ቀን ድረስ መጠበቅ የሚገባንን የነብስ እና የሥጋ ትንሣኤ እርሷ እስከ መጨረሻው ቀን ድረስ መጠበቅ ያልተገደደችሁ በዚሁ ምክንያት ነው።

ኢየሱስ ወደ እዚህ ምድር መቶ ተስቃይቶ ተሰቅሎ መሞቱን እና በሦስተኛው ቀን ከሙታን መነሳቱን በሚዘከርበት የእርገት ቀን መካከል እና ማሪያም ወደ ሰማይ የፈለሰችበት አጋጣሚዎች ግን የተለያዩ ሁኔታዎች እንደ ሆኑ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ጠንቅቀን እንድንረዳ አደራ ትለናለች። የእግዚኣብሔር ልጅ የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣  ሞትን ድል ነስቶ ወደ ሰማይ የወጣው በመለኮታዊ ኃይሉ አማክይነት ሲሆን ነገር ግን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያ ወደ ሰማይ የፈለሰቺው በእግዚኣብሔር መለኮታዊ ኃይል እንደ ሆነ ልብ ሊባል ይገባል።

የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ በቁጥር 966 ላይ “በመጨረሻም ንጽሕት ድንግል ማሪያም ከአዳም ኃጢኣት ሁሉ ተጠብቃ የምድራዊ የሕይወቷ ጉዞ ሲያበቃ በነብስ እና በሥጋ ወደ ሰማያዊ ክብር ተወሰደች። የጌቶች ሁሉ ጌታ ከሆነውና ኃጢኣትንና ሞትን ካሸነፈው ከልጇ ጋር አንድነቷ ይበልጥ የተሟላ መሆንኑን ለመመስከር በሁሉም ነገሮች ላይ ንግሥት ሆና በጌታ ከበረች”።  የብፅዕት ድንግል እርገት በልጇ ትንሣኤ ያደረገችሁ ልዩ ተሳትፎ ከመሆኑም በላይ የሌሎች ክርስቲያኖች ተስፋ ነው” በማለት ቀደም ሲል የተጠቀሰውን ማብራሪያ ያጠናክራል።

 

 

 








All the contents on this site are copyrighted ©.