2016-05-10 10:18:00

በሚያዚያ 29,2008 ቅዱስነታቸው በጳውሎስ ስድስተኛ የስብሰባ አዳራሽ ‘ሕክምና ለአፍሪካ’ ከተሰኘው የበጎ ፈቃድ ማሕበር አባላት ጋር በተገናኙ።


ቅዱስ አባታችን ፍራንቸስኮ በሚያዚያ 29,2008 በጳውሎስ ስድስተኛ የስብሰባ አዳራሽ ለተገኙ እና እንደ አውሮፓዊያ የቀን አቆጣጠር ከ1950 ዓ.ም. ጀምሮ ለአፍሪካ የሕክምና እርዳታ በመለገስ ለሚታወቀው ‘ሀኪሞች ለአፍሪካ’ ከተሰኘው የበጎ ፈቃድ ማሕበር ከተውጣጡ አባላት ጋር በተገናኙበት ወቅት “የጤና ሽፋን እጥረት ባለበት አፍርካ የሕክምና አገልግሎት በመስጠታቸሁ እናንተ የቤተ ክርስቲያን መገለጫ እንደሆነች እራሷዋን ዝቅ አድርጋ በጣም ደካማ ሰዎችን እንደ ምትንከባከብ አንዲት እናት ናችሁ” ማለታቸው ተገለጸ። 

በሁጋንዳ፣ በታንዛኒያ፣ በሞዛንቢክ፣ በአንጎላ፣ በኢትዮጲያ፣ በደቡብ ሱዳን እና በሴራሊዮን በመገኘት የበጎ ፍቃድ የሕክምና አገልግሎት የሚሰጠው ‘ሕክምና ለአፍሪካ’ የተሰኘው ማሕበር በተፈጥሮ እና በሰው ሰራሽ ችግር የሚነሱ በሽታዎችን በማከም ሰዎች በሕክምና እጥረት የሚደርስባቸውን መከራ በተለይም ደግሞ በጣም አጣዳፊ የሆኑ ወረርሽኞችን በማከም የእራሱን ከፍተኛ አስተዋጾ እያደረገ መሆኑም በእለቱ ተወስቱዋል።

ይህ ‘ሀኪሞች ለአፍሪካ’ የተሰኘው ማህበር ለ65 ዓመታት ያህል የበጎ ፈቃድ የሕክምና አገልግሎት በአፍሪካ በመስጠት እውቅናን ያተረፈ ማሕበር ሲሆን ከአንድ ሺ በላይ የሚሆኑ የበጎ ፍቃድ የሕክምና አባላትን በጣም ድኸ ወደ ሚባሉ የአፍሪካ ሀገራት በመላክ የሕክምና አገልግሎት እየሰጠ እንደ ሚገኝ የተገለጸ ሲሆን በእለቱም በጳውሎስ ስድስተኛ አዳራሽ ለተገኙ  ከዘጠኝ ሺ በላይ  ለሚሆኑ የህክምና አባላት እና ነርሶች  በከፍተኛ ደስታ ተሞልተው ሰላምታ ያቀረቡት ቅዱስነታቸው “የህክምና አገልግሎት ማግኘት የሰው ልጆች ሁሉ መሰረታዊ መብት ነው” ማለታቸውም ታውቁዋል።

“በጣም መሰረታዊ ሊባል የሚችል የጤና አገልግሎት በተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች በተለይም በአፍሪካ  አሁኑም ቢሆን እጥረት እንዳለ ይታያል” ያሉት ቅዱስ አባታችን “አሁን ባለው ሁኔታ መሰረት በእነዚህ ድኸ ሀገሮች የጤና ሽፋን ለሁሉም የተሰጠ መሰረታዊ የሰው ልጆች መብት እንደ ሆነ ሳይሆን የሚቆጠረው ለጥቂቶች ብቻ የተሰጠ የቅንጦት ነገር ተደርጎ እየተቆጠረ እና በጣም ድኸ የሚባሉ የማሕበረሰብ ክፍሎች ለሕክምና አገልግሎት ገንዘብ መክፈል ባለመቻላቸው በጣም ወሳኝ እና መሰረታዊ የሚባሉ ሕክምናዎችን እንኳ ማግኘት አለመቻላቸውን ” ቅዱስ አባታችን ፍራንቸስኮ ገልጸዋል።

 “እናንተ” አሉ ቅዱስ አባታችን “ብዙ ሺ ማይልሶችን በመጓዝ እነዚህን በችግር ላይ የሚገኙ የማሕበረሰብ ክፍሎችን እንደ ደጉ ሳምራዊ ሰው በችግር ላይ የሚገኘውን ዓላዛርን ለመርዳት መሄዳችሁ የሚያሳየው፣ በበለጸጉት እና በድኾች ሀገሮች መካከል ያለውን በር መክፈታችሁን ነው” ብለው “የከፈታችሁት ቅዱስ ሊባል የሚችል በር እናቶች በወሊድ ጊዜ በሰላም እንዲገላገሉ ያስቻለ እና ለልጆቻቸው ጤና ከፍተኛ አስተዋጾ እያደረጋችሁ  ትገኛላችሁ” ብለዋል።

 “በፍሪካ ብዙ እናቶች በወሊድ ወቅት ሕይወታቸውን ያጣሉ፣ ብዙ ሕጻናት አንድ ወር እንኳን ሳይሞላቸው በተመጣጠን ምግብ ማነስ ምክንያት እና በተለያዩ ወረርሽኞች ምክንያት የሞት ሰለባ ይሆናሉ” ያሉት ቅዱስ አባታችን “በእዚህ በሀዘን እና በስቃይ በተጎዳ ማሕበረሰብ ውስጥ ልክ እንደ ኢየሱስ አለኝታነታችሁን በማሳየት ከእነርሱ ጋር አብራችሁ እንድትቆዩ አበረታታችኋለው” ብለው “እያበረከታችሁ ያላችሁት አገልግሎት ‘የታመሙትን ፈውሱ’ ከሚለው የወንጌል መርሕ ጋር የሚመጣጠን እና እናት እንደ ሆነች ቤተ ክርስቲያን እራሷን ዝቅ አድርጋ በከፋ ችግር ላይ የሚገኙትን ሰዎች እንደ ምትንከባከብ የሚያሳይ ነጸባርቆች ናችሁ” ብለዋል።

“አፍሪካ” አሉ ቅዱስነታቸው አጽኖት ሰጥተው “አፍሪካ፣ በቆራጥነት እና እንዲሁም ብቃት ባለው መልኩ ምርምሮችን እና አዳዲስ ነገሮችን መፍጠር የሚያስችለውን ጉልበት ያገኝ ዘንድ ቀጣይነት ባለው መልኩ ሊታገዝ ይገባዋል” ብለው “አፍሪካም በአንጻሩ ለለጋሾች ግልጽነትን እንዲያሳዩ እና ለሕዝብ አስተያየት ጆሮዎቻቸውን መክፈት ይጠበቅባቸዋል” ብለዋል።

በመጨርሻም “እናንተ ከአፍሪካዊያን ጋር የምትሰሩ ሐኪሞች እንጂ ለአፍሪካ የተላካችሁ ሐኪማች አድርጋችሁ እራሳችሁን መቁጠር እንደ ማይገባ ማወቅ በጣም አስፈላጊ ነው” ብለው “በምትሰጡት አገልግሎት ሁሉ አፍሪካዊያንን በለውጥ ጎዳና ላይ ይራመዱ ዘንድ ማገዝ እና በተለይም ደግሞ የአከባቢውን አብያተ ክርስቲያናትን እና  መንግሥታትን ያማከለ የጋራ ኃላፊነት እንድታጎለብቱ ያስፈልጋል” ብለው “አንድ ቤተ ክርስቲያን በከፍተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙትን ሰዎች የምታክም ክሊንክ ሳትሆን፣ ነገር ግን እንደ ማነኛውም ተራ ሆስፒታል እንደ ሆነች በማሰብ ይህንን የጀመራችሁትን መልካም ተግባር በታላቅ ብርታት መቀጠል እንደ ሚጠበቅባቸው” አሳስበው ንግግራቸውን አጠናቀዋል።

 








All the contents on this site are copyrighted ©.