2013-12-07 10:55:28

ሰንበት ዘመጻጉዕ 2006 ዓ.ም 12/8/2013)


መዝሙር፡ ይቤሉ እስራኤል ኢርኢነ ወኢሰማዕነ. . . .
ንባባት፡ 2ቆሮ. 4:1-12፥ 1ዮሓ፡ 5፡11-ፍ፥ ግ.ሓ. 4:14-22፥ ዮሓ. 9፡13-25።
ስብከት፡ ደቂቀ እጓለ እመሕያው እስከ ማእዜኑ ታከብዱ ልበክሙ ለምንት ታፈቅሩ ከንቶ ወተሐሱ ሐሰተ፥ አእምሩ ከመ ተሰብሓ እግዚአብሔር በጽድቁ። መዝ.4፡2።
RealAudioMP3
“ጌታ ሆይ አምንበት ዘንድ እርሱ ማን ነው? ሲል ጠየቀ”፡፡ (ዮሐ 9፡36)በዚህ ሰንበት የምናዳምጠው የዮሐንስ ወንጌል 9፡1-41 ሲሆን ስለ አንድ ማየት ለተሳነው ሰው ስለተደረገለት ተአምራት ይናገራል፡፡ ይህ ሰው ዐይኑ እንደበራለት እንጂ ይህን ድንቅ ነገር ያደረገለትን ወዲያው ሊያየውም ሆነ በርሱ ማመኑን መግለጽ አልቻለም ነበር፡፡ ስለዚህ ያዳነውን ኢየሱስን ራሱን ጠየቀው፡፡ ልብ ብለን ካየን ግን የመጀመሪያ ጥያቄ አቅራቢና ይህን ሰው ወደ እምነት የጋበዘው ራሱ ክርስቶስ ነበር፤ “በሰው ልጅ ታምናለህን?” (ዮሐ 9፡35) በዓለም ላይ፣ በጨለማ ላይ፣በሰይጣን እኩይ ተግባር ላይ፣ በበሽታ ላይ፣ በተወሳሰበ የሕይወት እንቆቅልሽ እና ለተለያዩ ጥያቄዎች ሁሉ ምላሽ መስጠት በሚችለው የሰው ልጅ ታምናለህን?
መጀመሪያ ሰውየው ይህን ጥያቄ መመለስ አልቻለም ነበር ምክንያቱም በወቅቱ በነበረው ግርግር ውስጥ ኢየሱስን አላየውም አልለየውም ነበርና፤ እኛም አንዳንዴ በብዙ ጭንቀት ውስጥ ስንሆን የራሳችንን ጉዳይ ብቻ ስናዳምጥ ኢየሱስን እንስተዋለን፤ ድምጹ ይጠፋናል፡፡ ይህን ጌታ መልሶ ማግኘት ግን ብዙም አያዳግትም፡፡ ለዳነው ሰው የሰጠው መልስ በቂ ነው፤ “በፊት ማየት አትችልም ነበር አሁን ግን አይተኸዋል፤ ማየት ብቻም አይደለም በፊትህ ቆሞ የሚያነጋግርህም እርሱ ነው” አለው፣የምሥራች ነገረው፡፡ አንዳነዴ እኛም ክርስቶስ በውስጣችን ሆኖ በመንፈስ ሲያናግረን ድምጹን ለመለየት እንቸገራለን፡፡
ልብ ብለን ካስተዋልን የዚህ ሰው እምነት ደረጃ በደረጃ ነው እየጨመረ የሔደው፤ ዐይኖቹ ከመከፈታቸው በፊት ኢየሱስንም ሆነ ስላደረጋቸው ድንቅ ነገሮች በጆሮ ስሚ ብቻ ላይ ነበር እምነቱ የተመሰረተው፣ ይህ የምጀመሪያ ደረጃው ነው፤ በሁለተኛ ደረጃ ይህ ሰው ማመኑን በመታዘዙ ገለጸው፣ “በሰሊሆም መጠመቂያ ሔደህ ታጠብ” ሲባል ወዲያው ነው የሔደው (ዮሐ 9፡7)፡፡ በመጨረሻም “ቆሞ የሚያነጋግርህ እርሱ ነው፣የፈወሰህ እርሱ ነው” በተባለ ጊዜ ወዲያው ነው እምነቱን የገለጸው፣በቃሉም ሆነ በስግደቱ (ዮሐ 9፡38)፡፡
ክርስቶስ ዛሬም ይህንኑ ጥያቄ ለዘመኑ አማኞች ያቀርባል፤ ምን ዓይነት መልስ ነው የምንሰጠው? አንዳነዴ እናምናለን ወይም የእምነት ዓይናችን ብሩኅ ነው ብለን በተራ መታበይ ተሞልተን ይሆን ብዬ ራሴን እጠይቃለሁ፤ ከእኔ በላይ አማኝ የለም ብለን ለመናገር የምንደፍርበት አጋጣሚም አይጠፋም ይሆናል፤ ይህ ዓይነቱ መንፈስ ግን በክርሰቶስ ፊት ረብ እንደሌለው በቃሉ አረጋግጧል እንዲህ ሲል “ዕውሮች እንዲያዩ፣የሚያዩ እንዲታወሩ ለፍርድ ወደዚህ ዓለም መጥቻለሁ” (ዮሐ 9፡39)፡፡
ወደ እምነትና ወደ ሕይወት ለመምጣት፣ለመመለስ፣የመዳኛ መንገድንም ለመያዝ አሁንም ጊዜ አለ፣ በአዲስ መንፈሳዊነት ለመራመድ በኋላም ምስክርነት ለመስጠት፣ የአማኞች እና የጻድቃን ጉባኤ አባል ለመሆን አሁንም ዕድሉ አለ፡፡ ዐይነ ስውር የነበረው ስለ እውነት ስለመሰከረ ከክፉዎች ማኅበር፣ከምኩራብ ሲባረር ሜዳ ላይ አልቀረም ወደ ክርሰቶስ እና ወደ ጻድቃን ማህበር ገባ ምክንያቱም አዳኝ በሆነው መሲህ አምኗልና፡፡
የእግዚአብሔር አብ የእግዚአብሔር ወልድ የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሰላም እና ቡራክ ከሁላችሁ ጋር ይሁን፡፡ አሜን፡፡
ሠላም ወሰናይ

አባ ዳዊት ወርቁ
ዘማኅበረ ካፑቺን








All the contents on this site are copyrighted ©.