Home Archivio
2010-01-29 14:16:07
የተባበሩት የአሜሪካ መንግሥታት እና ካሪታስ ኢንተርናዚዮናሊስ
በሃይቲ በርእደ መሬት ለተጎዳው ህዝብ ከተባበሩት የአሜሪካ መንግሥታት ብፁዓን ጳጳሳት ምክር ቤት እና ከካሪታስ ኢንተርንዚዮናሊስ የሰብአዊ እርዳታ እየቀረበ መሆኑ ካቶሊክ ኔውስ ሰርቪስ የተሰኘው የዜና አገልግሎት አስታወቀ።
በተባበሩት የአሜሪካ መንግሥታት የሳን ኤንቶንይ ሊቀ ጳጳስ እና የተባበሩት የአሜሪካ መንግሥታት ብፁዓን ጳጳሳት ምክር ቤት የኅብረ ባህል ድርገት ሊቀ መንበር ብፁዕ አብነ ኾሰ ሆራሲዮ ጎመዝ በሃይቲ የተከሰተው ርእደ መሬት ባስከተለው የሞት እልቂት ካህናት የዘርአ ክህነት ተማሪዎች ገዳማውያን ደናግል አለማውያን ምእመናን የሞት አደጋ እንደደረስባቸው በማስታወስ፣ ሁለት አበይት ካቴድራሎች፣ አምስት አቢያተ ክርስትያን የካቶሊክ ትምህርት ቤቶች፣ የካቶሊክ የራዲዮ ጣቢያ ማሰራጫ ሕንጻ፣ የዘርአ ክህነት ትምህርት ቤቶች፣ የካቶሊክ የሕንጸት ማእከሎች መውደማቸው በመጥቀስ፣ ይኸንን ጉዳይ በተመለከተ የተባበሩት የአሜሪካ መንግሥታት ብፁዓን ጳጳሳት ምክር ቤት በመወያየት የአቢያተ ክርስትያን ገዳማት የዘርአ ክህነት ትምህርት ቤቶች እና የካቶሊክ ትምህርት ቤቶች ዳግም ለመገንባት በሚል እቅድ ድጋፍ እያቀረበ ነው እንዳሉ ሎሶርቫቶረ ሮማኖ የተሰየመው የቅድስት መንበር ዕለታዊ ጋዜጣ ትላትና ባወጣው ኅትመቱ አስታወቀ።
ካሪታስ ኢንተርናዚዮናሊስ 45 ሚሊዮን ኤውሮ ማሰባሰቡ ሲገለጥ፣ ይህ ደግሞ ለሃይቲ የመሠረት ልማት ዳግመ ግንባት እቅድ እንደሚውል ሎሶርቫቶረ ሮማኖ ያሰራጨው ዜና አመለከተ።
ይህ በእንዲህ እንዳለም የኩባ ካቶሊክ ቤተ ክርስትያን እና የአገሪቱ መንግሥት በርእደ መሬት ለተጠቃው ለሃይቲ ህዝብ ድጋፍ እያቀረበ መሆኑ ሲገለጥ፣ የኩባ የካሪታስ የተራድኦ ማኅበር ለሃይቲ የሰብአዊ እርዳታ ካቀረቡት የተራድኦ ማኅበራት ግንባር ቀደም መሆኑ ለማወቅ ተችለዋል።
All the contents on this site are copyrighted ©.